September 19 2020
በአዲስ አበባ በ400 ሚሊዮን ብር ወጪ እየተገነባ ያለው የእናቶችና ህፃናት ሆስፒታል ግንባታው ተጠናቆ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ስራ እንደሚጀምር ተገለፀ።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አዳነች አቤቤ አያት አካባቢ በግንባታ ላይ ያለውን የእናቶችና ህፃናት ሆሥፒታል ዛሬ ጎብኝተዋል።
የሆስፒታሉ መገንባት በከተማዋ በእናቶችና ህጻናት ሆስፒታል ህክምና አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ይስተዋል የነበረውን ችግር የሚያቃልል መሆኑን ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ሃላፊ ዶክተር ዮሃንስ ጫላ በበኩላቸው ከዚህ ቀደም የእናቶች እና ህጻናት ህክምና አገልግሎት ራሱን ችሎ የሚሰጠው የጋንዲ ሆስፒታል ብቻ መሆኑን ጠቅሰዋል።
የጋንዲ መታሰቢያ ሆሥፒታል ባሉት 89 አልጋዎች በቀን ከ900 በላይ ወላዶችን በማሰተናገድ ከባድ ጫና ያለበት መሆኑንም ገልጸዋል።
አሁን ግንባታው እየተገባደደ ያለው ሆስፒታል ግን 400 አልጋዎች ያሉት በመሆኑ ላቅ ያለ ጥቅም ይኖረዋል ብለዋል ዶክተር ዮሃንስ ።
በአዲስ አበባ አያት አካባቢ እየተገነባ ያለው ሆስፒታሉ በ23 ሺህ ካሬ ላይ ያረፈ ዘመናዊ ህንፃ መሆኑን የኮንስትራክሽን ቢሮ ምክትል ሃላፊው አቶ አፈወርቅ ንጉሴ ገልጸዋል።
አሁን ላይ የሆስፒታሉ ግንባታ 99 በመቶ መድረሱን ተናግረው ግንባታው ተጠናቆ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ወደ ስራ ይገባልም ብለዋል።
ሆስፒታሉ 14 የማዋለጃ ክፍሎችና 7 የኦፕሬሽን ክፍሎችን ያካተተ መሆኑም ታውቋል።
For More Health related Vacancies Click Here
To Get alerts of latest Health Related News Go-to Our Telegram Channel